Monday, September 19, 2016

ዩሱፍ ያሲን ሲቀልድ

        ሰሞኑን ዩሱፍ ያሲን የተባለ ኤርትሮ - ኢትዮጵያዊ ያሳተመውን መፅሃፍ አንብቤ ጨረስኩ። ድሮ በብእር ስም ጦቢያ መፅሄት ላይ ሲፅፍ አድናቂው ነበርኩ። "አሰባሳቢ ማንነት በአንድ አገር ልጅነት" ብዙ ጠቃሚ አሳቦችና መረጃዎችን ያቀፈ ድንቅ መፅሃፍ ቢሆንም፤ አፃፃፉ ወገብ ያጎብጣል። ፅሁፉ ደቃቅ ስለሆነ አይን ያሳምማል። ዞረም ቀረ መፅሃፉ ከነሙሉ ችግሩ የተከበረ መፅሃፍ ነው። ኖርዌጅያዊው የዙላ ከተማ ተወላጅ ጥሩ ፀሃፊ መሆኑን መካድ አይቻልም። የዩሱፍ ያሲንን መፅሃፍ ሳነብ በመካከሉ በሳቅ ፈነዳሁ። ዩሱፍ በአንድ መስመር የገለፃትን ቀልድ እኔ እንዲህ አቅርቤላችሁዋለሁ።


        በጥንት ዘመን በመናገሻ አውራጃ፣ ሰፊ ርስት ይዘው በቀላድ የመሬት ስሪት በጭሰኛ መሬት ያሳርሱ የነበሩ አንድ የታወቁ ባላባት ነበሩ። ነዋሪነታቸው በአዲ-ሳባ ነበር። የተነገረላቸው አዋቂ ነበሩ። በአድዋ ጦርነት ተዋግተው ጀብዱ ፈፅመዋል። ረጅም፣ ጠይም ኮስታራ ነበሩ። ፊታውራሪ አዝረጥርጤ ከበደ ይባላሉ።

        ምን ያደርጋል?
    
   ሞት አይቀርምና በህመም አረፉ። እናም በታላቅ ስነስርአት ስላሴ ተቀበሩ። ጃንሆይ ከነሚስታቸው፣ ከነጳጳሳቸው ቀብሩ ላይ ተገኝተው ነበር። ሟቹ ፊታውራሪ እመቤት የምትባል አንዲት ቆንጆ ደርባባ ሴት ልጅ ነበረቻቸው። በአባቷ ሞት ክፉኛ ተጎዳች። የፊታውራሪው  ሴት ልጅ ሃዘኗን እንድትረሳ መሳፍንቱ ብዙ ደክመውላታል። በርግጥም በዘመድ አዝማድ ጥረት ሃዘኗ ቀለላት። ቢሆንም ባገኘችው አጋጣሚ ሁሉ የአባቷን ስም ካላነሳች አይሆንላትም ነበር።
    
    አንድ ጊዜ የመኳንንት ዘር ከሆነ የቅርብ ዘመዷ ቤት የሰርግ ዝግጅት ለማገዝ ሄደች። ወይዛዝርቱ ተሰባስበው ስጋ እየከተፉ ያወጉ ጀመር። እንደተለመደው ታዲያ ከስጋው ጋር የሰው ስም እየተነሳ ይከተፋል፤ ይዘለዘላል። በመካከሉ ከወይዛዝርቱ አንዷ እንዲህ ስትል ወግ አመጣች፣

        "ባለፈው ሳምንት የሼኽ ሓሰን ዑመር አብደላ ሁለተኛ ሚስት ወንድ ልጅ ተገላገለች አሉ። እቴጌ መነን ለአራስ ጥሪ ሶስት የዱከም ሰንጋ እያስነዱ ሄደው ጠይቀዋታል ይባላል። እንደሰማሁት ከሆነ ሼሁ ለልጃቸው አሊ የሚል ስም ሰጥተውታል።"

        በዚህ ጊዜ የፊታውራሪ አዝረጥርጤ ሴት ልጅ ወይዘሮ እመቤት በድንገት ስጋ ትመትርበት የነበረውን ቢላ ቁጭ አድርጋ እንዲህ አለች አሉ፤

        "በአዝረጥርጤ ሞት! ሰው እንዴት ለልጁ አሊ ብሎ ስም ያወጣል?"


        ይህ የዘመናችን ምርጥ ቀልድ ሲነገር ከወይዛዝርቱ መካከል አንድም የሳቀ አልነበረም። አባባሉ ለፈገግታ እንደሚያበቃ እንኳ የጠረጠረ አልተገኘም። ምንም እንዳልተነገረ፣ አንዳች እንዳልተፈጠረ ሁሉ ወይዛዝርቱ ስጋ እየመተሩ፣ ወጋቸውን ቀጠሉ።        

5 comments:

Tesfaye said...

ማንበብህም፣ መተቸትህም ነፃ ፈቃድህ ነው፡፡ ማንም የሚሰጥህ ወይም የሚነሳህ አይደለም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እያስተዋልኩ የመጣሁት ጠባይህ ግን ግ...ርም እያለኝ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ በተለይም በኦሮሞ ሕዝብ ላይ ያለህ ተቆርቋሪነት ወደር እንደሌለው አድርገህ ታቀርብ የነበረው፣ በአንተ አባባል "በጭቁኑ" አማራና ("ከኢትዮአማራዎች" ለመለየት ነው)በኦሮሞ ሕዝብቦች መካከል ሊፈጠር የሚገባው በእኩልነት ላይ የተመሠረተ አገራዊ አጀንዳ ኢትዮጵያ የምትባለዋን አገር የወደፊት ዕጣ ፈንታ እንደሚወስንም ስታስተጋባ ነበር፡፡

ይሁንና የት ይደርሳል የተባለ ወይፈን ... እንደሚባለው በዚህ ጭንቅ ቀን፣ "እሳትና ጭድ" በተባሉት ሁለቱ ታላቅ ሕዝቦች መካከል "የአሸዋና የሲሚንቶነት" ነገር ሲፈጠር በጠራራ ፀሐይ እያየህ፣ ምናልባትም ከብዙ ጀሌ ኢትዮጵያውያን በተሻለ መረጃ እያለህ፤ ጊዜህን ግን የምታጠፋው እንጭፍጫፊ መሆነ ዝባዝንኬ ነው፡፡ አቶ ተመስገን ዘውዴ መለስን ተራ አተካራ ውስጥ ገብተህ ትዛቅጣለህ እንዳሉት ዓይነት መሆኑ ነው፡፡

በዚህ በአቶ የሱፍ ያሲን ጉዳይ ከርእሱ ጀምሮ የሰውየውን ሰብአዊ ቁመናና አእምሮአዊ ብቃት እንዘጭ አድርገህ አፈር ድቤ አብልተህ መልሰህ ልትክብ ትሞክራለህ፡፡ እንደ ሞያተኛ የሰውየውን ሰብአዊና አእምሮአዊ ማንነት ጥንብ ርኩስ ሳታወጣ በመጽሐፉ ይዘቱ ላይ ብቻ ሞያዊ የትችት ናዳህን ማዝነብ አይቻልህም ነበር?

አይ የገብረአብ ልጅ ተስፋዬ!
ተስፋዬ ነኝ፣ ከገነት ሆሎታ፡፡

Tech with Estif said...

THANK YOU!!! "THE BLACK SOIL OF ADHA"

Unknown said...

A good summary

Anonymous said...

U r name should be Devil

Anonymous said...

This time you must be burning inside! because the two big people of Ethio are back together!
Why are you not writing "Ye-Zarema Zimitta'!
You are the Black Devil of ADHA!... ተስፋዬ ገብረእባብ!የፉኝት ልጅ