Thursday, January 23, 2014

የሰለሙና ወጎች


ጊዜው ህዳር አጋማሽ ነበር - 2013

ረፋዱ ላይ ወደ ከረን የሚወስደውን መንገድ በመተው ወደ ዛግር አቅጣጫ ታጠፍን። ረጅም ጉዞ ስለሚጠብቀን ከወዲ ሓሬና ብዙ ወግ እንደማገኝ ርግጠኛ ነበርኩ። ከሚጠብቁኝ ወጎች መካከል፣ “የስደተኛው ማስታወሻ” ህትመት መቋረጥ፤ የጫልቱ ሚደቅሳ ግለ - ታሪክ ጉዳይ እና የመጪው ዘመን የኢትዮጵያ እጣ ፈንታ የግድ የሚነሱ ነበሩ። ሆኖም እንደሚጠበቀው በቀጥታ ወደነዚህ ርእሰ ጉዳዮች አልገባንም። በቅድሚያ ቀላል ወጎችን ተጨዋወትን።

“በ1970 የበልጉ ወራት ወጣት የኢህአፓ ታጋይ ሳለህ፣ በዚህ መንገድ በእግር ተጉዘህ ከሻእቢያ ተዋጊ ባታሊዮን ጋር ተቀላቅለህ እንደነበር ሰምቻለሁ። እውነት ነው?”

ወዲ ሓሬና ዘወር ብሎ ተመለከተኝ፣
“ይህን ማን ነገረህ?”
“አንተን በደንብ ከሚያውቅ የሻእቢያ ሰው ሰማሁ።”
“በሰለሙና በኩል ይዘኸኝ የመጣኸው ይህን ታሪክ እንዳስታውስ ብለህ ነው?”
“አይደለም። በሰለሙና ጫካ እና ጉም መካከል መጓዙን ትመርጣለህ ብዬ ነው።” 

የጀብዱ ፊልም የሚመስል ታሪክ እያጫወተኝ ተጓዝን።
የሰለሙና ጫካ መካከል ሁለት የዋህ ውሾች እስኪገጥሙን ድረስ በሰላም ተጉዘን ነበር። ወዲ  ሓሬና በዘመነ ደርግ ከጥቂት በላይ ጓደኞቹ እና ታናሽ ወንድሙ ከተገደሉ በሁዋላ ከአዲስአበባ ወደ አስመራ ኮበለለ። ከአስመራ ወደ ሻእቢያ ነፃ መሬት ከተሻገረ በሁዋላ፣ የትግራይን መሬት አስሶ፣ እንደገና ወደ ኤርትራ በመመለስ በናቅፋ - ቃሮራ በኩል በሻእቢያ የጭነት ሎሪ ተንጠላጥሎ ሱዳን ገባ። ከዚያም ወደ ለንደን እንዴት እንደተጓዘ ልብ የሚሰቅል ወግ አጫወተኝ። 

እንደ አንድ የኤርትራ ገበሬ ለብሶ፣ እንዳካባቢው የገጠር ሰዎች ዘንቢል ቢጤ ተሸክሞ ነበር የተጓዘው። የገጠር ልብስ የለበሰች ኤርትራዊት እናት አብራው ነበረች። በርግጥ ይህች እናት የገጠር ሴት አልነበረችም። አዲስአበባ ላይ መምህር የነበረች የአንዳርጋቸው እናት ጓደኛ ነበረች። የጓደኛዋን ልጅ ህይወት ለማትረፍ የራሷን ህይወት አሳልፋ እየሰጠች ነበር። የደርግን ኬላ ከተሻገረች በሁዋላ የፅጌን ልጅ ለሻእቢያ አስረክባ ወደ አስመራ ተመለሰች። የሻእቢያ ታጋዮች አንዳርጋቸውን ከተረከቡ በሁዋላ እንደሚሰበር እንቁላል ተንከባክበው ይዘውት ሌሊቱን በዚህ በፍልፍል ሰለሙና መንገድ ተጉዘዋል። ይህ ታሪክ ከተፈፀመ በትክክል 35 አመታት አልፎታል። አንዳርጋቸው አንዳንድ ቦታዎችን እያስታወሰ ነገረኝ። ወኪ እና ዛግር በፍፁም አልጠፉትም።  

“ይህን ታሪክ በሚዲያ ተናግረህ አታውቅም።” አልኩ።
“የጠየቀኝ አልነበረም።” አለ። አያያዘና አከለበት፣ “…ምስጢር ግን አይደለም።”
 

• • • 

ከአንዳርጋቸው ጋር በሰለሙና ጥቅጥቅ ጫካ ማህል በመኪና ስንጓዝ ሁለት የዋህ ውሾች ገጥመውን ነበር። ውሾቹ ከመምጣታቸው በፊት ወያኔ ወደ ግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል አስርጎ ስላስገባው ቅጥረኛ ነፍሰ-ገዳይ እያጫወተኝ ነበር። ወያኔዎች በአንዳርጋቸው የመገደል ዜና የፈንጠዝያ ሻምፓኝ ለመክፈት የሚለብሱትን ልብስ ሲመርጡ በምናብ እየሳልኳቸው ነበር። የምንግባባበትንም ሆነ የማንግባባበትን ብዙ ርእሰ ጉዳዮች እያነሳን በሰለሙና ጫካ መካከል ጉዞ ቀጠልን።  

አንስተን ከተወያየንባቸው ጉዳዮች መካከል የጫልቱ ሚደቅሳ ግለ - ታሪክ አንዱ ነበር። ነፃነት አሳታሚ ሊያፍነው የሞከረው “ምእራፍ 7” በግልባጩ ይበልጥ ተነባቢ በመሆኑ ከዋና አላማዬ አንፃር ሲመዘን ትርፍ እንጂ ኪሳራ አልገጠመኝም። አንዳርጋቸው በጫልቱ ታሪክ መታተም ላይ ተቃውሞ እንደሌለው በግል ገልፆልኛል። ቢሆንም ከአሳታሚው ጋር ባለው ግንኙነት የውሳኔው አካል ነበር ማለት ይቻላል። ይህ ሁኔታ ግን ግንኙነታችንን አላሻከረውም። ርእሰ ጉዳዩን በመተው ግንኙነታችን ቀጥሎአል። ነፃነት አሳታሚ ‘ጫልቱ እንደ ሄለን’ በተባለው ትረካ ምክንያት፣ “የስደተኛው ማስታወሻ”ን ህትመት በማቋረጡ ያዘኑ ኦሮሞ ወገኖች፣ በዋሽንግተን ዲሲ፣ በኖርዌይ እና በካናዳ ገቢ የማሰባሰብ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት መፅሃፉን ለማሳተም የሚበቃ ያህል ገንዘብ አሰባስበዋል። ይህን ለአንዳርጋቸው ስነግረው ሲታተም አንድ መፅሃፍ እንደሚገዛ አረጋገጠልኝ። በፓውንድ ሳይሆን በናቅፋ እሸጥለታለሁ። በርግጥ የደራሲ ዋነኛ ትርፍ መፅሃፍ መሸጥ ሳይሆን መነበብ መቻል ነው። መፅሃፍ ፅፎ ያልተነበበለት ደራሲ በቁም እንደሞተ ይቆጠራል። ያም ሆኖ የዳያስፖራ ኦሮሞ ኮሚኒቲ አባላት ባዋጡት ገንዘብ “የስደተኛው ማስታወሻ”ን ለማሳተም ከኦቦ ገረሱ ቱፋ እና ከጓደኞቹ ጋር እየሰራን እንገኛለን።  

የሰለሙና ሽቅቡ ተራራና ሽምጥ ገደሉ ሙሉ በሙሉ በጉም ተሸፍኖ ነበር። መብራት አብርተን ነበር የምንጓዝ። አልፎ አልፎ ግን ጉሙ ይገለጣል። ጉሙ ሲገለጥ አማዞን ብብት ውስጥ ያለን ይመስል ከላይ እና ከታች በጫካው እንሸፈናለን። በጉም ስንሸፈን ደግሞ በአይሮፕላን የምንጓዝ ይመስላል። በዘመነ ደርግ የኢትዮጵያ ወታደሮች ይህን ቦታ፣ “የሻእቢያ ብርድ ልብስ” የሚል ቅፅል ስም ሰጥተውት እንደነበር ሰምቻለሁ።  

ጉሙ ውስጥ እየገባንና እየወጣን ስንጓዝ ሁለት የመንደር ውሾች በድንገት መኪናችንን ከበቧት። ሽማግሌ እና ወጣት ውሾች ናቸው። ሽማግሌው ውሻ አፉን ከፍቶ እየጮኸ ጥቂት ከሮጠ በሁዋላ ከጎዳናው ወጣ። ወጣቱ ውሻ ከመኪናችን እኩል እየጋለበ ብዙ ርቀት ተከተለን። ቅልጥሙን ለሚያይ አቦሸማኔ እንጂ ውሻ አይመስልም። ፍሬን ስይዝ የመኪናውን ጎማ ለመንከስ ይጠጋል። ነዳጅ ስረግጥ ጎን - ጎን ይጋልባል። በመኪናው ጎማ ጥቂት ብነካው ተንከባሎ ገደል በገባ ነበር። አጥንቱ እንኳ ባልተገኘ። ውሻው እራሱን የሚጎዳውን ድርጊት በመፈፀም ላይ እንዳለ አልተረዳም። በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለን አንዳርጋቸው መከረኝ፣ 

“አትቁም። ዝም ብለህ በፍጥነት ንዳ!” 

መኪናዋን ረገጥኳት። ወጣቱ ውሻ ወደ ሁዋላ ቀርቶ አቦሬውን ሲከፍት ጥቂት ሰማሁት። ቁልቁለቱን ጨርሰን አቀበቱን ስንያያዝ የውሻው ድምፅ ከጆሮዬ ራቀ። በርግጥ ጩኸቱን ቀጥሎ ሊሆን ይችላል። ለእኔ ግን አልተሰማኝም። ውሾቹን አልፈን አቀበቱን ስንያያዝ ዳገቱ ላይ ግመሎች ገጠሙን። በእርጋታ በአጠገባቸው አለፍን። ዘወር ብለው እንኳ አላዩንም። 

• • • 

እነሆ! የኔ የህይወት ጥሪ መፅሃፍ መፃፍ እንደመሆኑ ለምሰራው ስራ መረጃ ለማግኘት የተለያዩ መንገዶችን እየለዋወጥኩ እጓዛለሁ። ዛሬም በሌላ መንገድ ከፅጌ ልጅ ጋር እያወጋን ጉዞ ላይ ነኝ…  

“ህመምተኛው ተሻለው?” ስል ጠየቅሁት።
“በማገገም ላይ ነው።” አለኝ።

ከሁለት ሳምንታት በፊት አንድ የግንቦት 7 ታጋይ ታሞ ሆስፒታል ገብቶ ህክምና እየተከታተለ ነበር። ብዙውን ጊዜ ከበረሃ ወደ አስመራ ሲመለስ ከአንዳርጋቸው ጋር እንገናኛለን። ነፃ ጊዜ ሲያገኝ ይደውልልኝና ቡና እንጠጣለን። አንድ ቀን ግን ያለቀጠሮ በአጋጣሚ አስመራ እህል ተራ ተገናኘን። ሳያየኝ ከጀርባው እንደ ቀዌሳ ድምፅ አጥፍቼ ተጠጋሁት፣ 

“ግንቦት 7 እህል ተራ ምን ያደርጋል?” ብዬ ስናገር ፈጥኖ ዞረ።
እኔ መሆኔን ሲያውቅ ወቅታዊ ቀልድ ቀለደ፣
“እየሰለልከኝ ነው እንዴ?”
በጣም ስቄ መልስ ሰጠሁ፣
“አለማችን የምትመራው በስለላ ተቋማት ነው።”

እየተቀላለድን አንዳርጋቸው ሸመታውን ቀጠለ። ሶስት ኪሎ ዳጉሳ፣ አንድ ኪሎ ሽምብራ እና ግማሽ ኪሎ ባቄላ ሲገዛ ቆሜ ተመለከትኩት መጀመሪያ በጣም ተገረምኩ በመቀጠል ግን እነዚህን ጥራጥሬዎች ለምን እንደፈለጋቸው ለማወቅ ፈለግሁ። በርግጥ አንዳርጋቸው ቆሎ እንደሚወድ ስለማውቅ የሽምብራና የባቄላው ገብቶኝ ነበር። አንዳርጋቸው ዳጉሳ መግዛቱ ግን በውነቱ አልገባኝም ነበር። ዳጉሳ ጠላ ለመጥመቅ የሚያገለግል ነው። እና ስለዳጉሳው ስጠይቀው አብራራልኝ፣ 

“ዳጉሳ ከሆነ ቅጠል ጋር ተቀላቅሎ፣ በቂጣ መልክ ተጋግሮ የሚሰራ ባህላዊ መድሃኒት አለ። ለታመመው አባላችን ነው የገዛሁትአለኝ።
“የሚላላክ ሰው የለህም እንዴ ታዲያ?”
“አስመራ ሰው የለንም። ሁሉም ግንባር ናቸው።” 

• • • 

በሰለሙና መንገድ ላይ ስንጓዝ ከአንዳርጋቸው ጋር አንስተን የተወያየንበት አንድ አነጋጋሪ አጀንዳ ነበር። የሚቀጥለው ዘመን ኢትዮጵያ ምን ትመስላለች? ወይም ኢትዮጵያ ወዴት ታመራለች? አሊያም የኢትዮጵያ እጣ ፈንታ ምን ይሆናል? እንዲህ ያሉ ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉ።  

“በመጨረሻ ይህን ጥያቄ የሚመልሱት ኢትዮጵያውያን ብቻ ናቸው።” ይባላል! እንላለን! እውነት ለመናገር ግን የሚባለው ሁሉ እውነት አይደለም። የአካባቢውም ሆኑ ሃያላኑ አገራት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በዚህ አካባቢ የፖለቲካ ጉዞ ላይ እጃቸውን ማስገባታቸው አልቀረም። በዚያም ተባለ በዚህ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሃይሎች የሃይል አሰላለፍ የተዘበራረቀ ነው። ከዚህ ሁሉ የፉገራ ዴሞክራሲና የቁጭ በሉ ምርጫ በሁዋላ እንኳ፣ ኢትዮጵያ ፈንጂ ላይ የተቀመጠች አገር መሆኗ እውነት ሆኖአል። የአንድነት ሃይሎች ራሳቸው በአንድ የአመለካከት መስመር ላይ አይጓዙም። በብሄር የተደራጁ ወገኖችም ቢሆኑ ግባቸው ለየቅል ነው። ህወሃት፣ ኦነግ እና ግንቦት 7 ከፊታችን አሉ እንበል። በርግጥ አርበኞች ግንባር፣ ኦብነግ፣ መድረክ፣ ዴምሕት፣ ኢህአፓ እያሉ መቀጠልም ይቻል ይሆናል። የመጪውን ዘመን የሃይል አሰላለፍ ለመተንበይ የፖለቲካ ድርጅቶች በይፋ በሚታወቅ ፕሮግራማቸው ሳይሆን፣ በድብቁ እና በእውነተኛው አመለካከታቸው ለያይቶ ማየቱ ይበጃል።  

የህወሃት አክራሪ ብሄርተኞች ስልጣናቸውን በሰላም ለማስረከብ በፍፁም ፈቃደኛ አይደሉም። የኢትዮጵያን አንድነት የሚፈልጉት ስልጣን በእጃቸው እስካለ ድረስ ብቻ ነው። በአስገዳጅ ሁኔታ የኢትዮጵያን ማእከላዊ ስልጣን የሚያጡ ከሆነ ያዘጋጁት የመጠባበቂያ አማራጭ ይዘዋል። ለአማራጩ የሚያገለግሉ ስራዎችን ሲሰሩ ከወዲሁ እያየን ነው። አብርሃም ያየህ እንደጠቆመን “ሰሜን ኢትዮጵያ” ስለተባለች አገር ህልም እያለሙ ነው። “የሰሜን ኢትዮጵያ”ን ዋና ከተማ “መቐሌ” ማድረግ ይፈልጋሉ። እንደ ምኞታቸው ከሆነ “የሰሜን ኢትዮጵያ” የግዛት ክልል ሙሉ ትግራይን፣ አፋርን፣ ሰሜን ወሎን፣ ሰሜን ጎንደርን፣ ሁመራና መተማን ከተቻለ ከዚያም የሰፋ መሬት የያዘ ይሆናል። ወልድያን ግን ህወሃት በፍፁም መተው አይችልም። ከጅቡቲ የሚነሳው ባቡር ወደ መቐሌ ሲጓዝ ወልድያን ረግጦ የሚያልፍ በመሆኑ ወልዲያ ለትግራይ ቁልፍ መሬት ሆናለች። የህወሃት ሰዎች ዋልድባና ራስዳሸን ዙሪያ ማንዣበባቸው የዚሁ ፕሮጀክት አካል ይመስላል። 

“ደቡብ ኢትዮጵያ” የሚል አሳብ የሚያቀነቅን ወገን ደግሞ አለ። ይህን የሰማሁት ከኦሮሞዎች አካባቢ ነው። በርግጠኛነት ‘የኦነግ አጀንዳ ነው’ ማለት አልችልም። ‘የቡድን አሳብ ነው’ ለማለትም መረጃ የለኝም። ግለሰቦች ግን አሳቡን ያቀነቅኑታል። በቅርብ ከማውቃቸው የኦነግ አባላት ጋርም በጉዳዩ ላይ ተወያይተንበታል። ጉዳዩ ሲጀመር “ኦሮሚያን መገንጠል የመጨረሻ ግብ መሆን የለበትም።” ይላሉ። በአንፃሩ ደግሞ “ኢትዮጵያን ጠቅልለን የመግዛት ፍላጎት የለንም” ይላሉ። በዚህ መካከል “የደቡብ ኢትዮጵያ” አሳብ ብቅ ይላል። የኦሮሞ ህዝብ ከደቡብ እና ከምእራብ ህዝቦች ጋር ተመሳሳይ የጭቆና ታሪክ አለው። ኢትዮጵያ የሚለው ስም “ጠይም” ወይም “ጥቁር” ማለት ከሆነ ደግሞ ቃሉ ለኦሮሞና ለደቡቦች ይቀርባል። ስለዚህ ከደቡብ ብሄረሰቦች፣ ከኦጋዴኖች፣ ከወሎ፣ ከሃረሪዎች፣ ከቤኒሻንጉልና ጋምቤላ ጋር ግንባር በመፍጠር፣  ዋና ከተማቸውን “ፊንፊኔ” በማድረግ “ደቡብ ኢትዮጵያ” የተባለች አገር መመስረት እንደሚችሉ ይናገራሉ። ይህ አሳብ ከእነ ሌንጮ ለታ አዲስ እንቅስቃሴ ጋር ይቀራረባል። የኦነግን ባንዴራ ይዘው ወደ ኢትዮጵያዊነት የመመለሳቸው ምስጢር ብዙዎችን ግራ አጋብቶ ቆይቶአል። መለስና ሌንጮን ሊያግባባቸው ይችል የነበረ አጀንዳ ይህ ይሆን? በርግጥ “ደቡብ ሱዳን” የሚለው አገር መምጣትና “ኦሮሚያ የሚለውን ራእይ ለይቶ ተግባራዊ የማድረጉ እድል ጠባብ ነው” ተብሎ መታሰቡ  ወደዚህ አሳብ ጎትቶአቸው ሊሆን ይችላል። 

እዚህ ላይ የኦቦ ሌንጮ ለታ መንገድ ለብቻው ተነጥሎ መታየት ስለመቻሉ በርግጠኛነት መናገር አልችልም። ሌንጮ በሚቀጥለው የወያኔ ምርጫ ለመሳተፍ ወስኖ፣ ሻንጣውን በማሰር ላይ መሆኑ ተሰምቶአል። ሌንጮ ወደ አዲስአበባ ተመልሶ ዳዴኡኦን (OPDO) በወደቀ ዋጋ ሊገዛው መዘጋጀቱን “የቤተመንግስት ሹክሹክታ” በሚል ርእስ ከሁለት አመታት በፊት ፅፌ ነበር። ይኸው ጊዜው ደረሰ። በርግጥ ሌንጮ ለታ ደረቱ ላይ Odaa ያለበትን፣ “አሸባሪ” ተብሎ የተፈረጀ ባንዴራ ፊንፊኔ ላይ ማውለብለብ ከቻለ፣ ቢያንስ ኦነግን እንደ ፈጣሪ የሚያመልከው ወጣት ኦሮሞ ጊዜያዊ መጠለያ ያገኛል።

ያልተመለሱልኝ ጥቂት ጥያቄዎች ግን አሉ።

በርግጥ ሌንጮ ወደ አዲሳባ እንዲመለስ አሜሪካኖች ወያኔን አስገድደዋል? የብአዴን ጥቁር አማሮችን ከፍ ከፍ ማለት ለማስተንፈስ ወያኔ ከሌንጮ ጋር ታክቲካዊ ውል ፈፅሞ ይሆን? እንዲህ ላሉ ጥያቄዎችና ወሬዎች መልስ የሚሰጠኝ አገኛለሁ ብዬ አልጠብቅም። ጊዜ ሲያልፍ ፍሬው ከገለባ ይለያል።   

ሶስተኛው ግንባር “የአንድነት ሃይሎች” በአብዛኛው የአማራዎች ሲሆን፣ ከተለያዩ ብሄር ብሄረሰቦች ተቀላቅለው የተወለዱትን፣ ማለትም “ኢትዮጵያዊ” መባሉን ብቻ የሚመርጡትንም ጨምሮ ያቀፈ ነው። አማራ ያልሆኑ እንደ ቡልቻ ደመቅሳ፣ ነጋሶ ጊዳዳ፣ ሃይሉ አርአያ እና በየነ ጴጥሮስ ያሉ የፖለቲካ ሰዎች የሚመሯቸው ድርጅቶችም ከአንድነት ሃይሎች ማእቀፍ ውስጥ ይካተታሉ። መረራ ጉዲና ትክክለኛው አቋሙ በግልፅ አይታወቅም። ከሁለቱም ተቃራኒ ሃይሎች ጋር ተግባብቶ ዘልቆአል። የአንድነት ሃይሎች “የኢትዮጵያን የቀድሞ የግዛት ክልልና አደረጃጀት እንደነበረ አስጠብቀን፣ አማርኛ የመግባቢያ ብሄራዊ ቋንቋችን ሆኖ፣ ኢትዮጵያውያን ተብለን በጋራ መኖር እንችላለን” ይላሉ። በጥቅሉ ሲታይ የቀድሞው ቅንጅት እና ኢህአፓ የዚህ አመለካከት ዋነኛ ባለቤት ሊባሉ ይችላሉ። 

በሰለሙና መንገድ ላይ ስንጓዝ፣ ከላይ ያሉትን ነጥቦች ለአንዳርጋቸው አነሳሁለት። አስተያየቱን ለመሰንዘር ጊዜ አልወሰደበትም። በርግጥ እየቀለደ እንዲህ ብሎኛል፣ 

“መቼም የምናገረውን መፃፍህ ስለማይቀር ግንቦት 7ን ወክዬ እየተናገርኩ እንዳልሆነ አስምርበት።” 

የህወሃት አክራሪ ብሄረተኞች የኢትዮጵያን አንድነት የሚፈልጉት ማእከላዊው ስልጣን በእጃቸው እስካለ ድረስ ብቻ በመሆኑ ላይ አንዳርጋቸው ተስማማ። ስለዚህ “ሰሜን ኢትዮጵያ” በሚል ስምም ሆነ በሌላ ቃል አገር ለመመስረት ማለማቸው አዲስ ነገር አይደለም። የፖለቲካ ሰዎች ነን የሚሉ ጥቂቶች ቢመኙትም ከትግራይ ህዝብ ድጋፍ እንደማያገኙ ጨምሮ ገለፀ።  “ደቡብ ኢትዮጵያ” በሚል ማእቀፍ በአንዳንድ ኦሮሞዎች የሚቀነቀነውን አሳብም “realistic አይደለም።” ይለዋል። የደቡብ ህዝቦች በሰፊው ኢትዮጵያ ውስጥ በኢትዮጵያዊነት መኖርን እንደሚመርጡ አሰመረበት። 

በርግጥ አንዳርጋቸው አንዳንድ አዳዲስ አሳቦችን ነግሮኛል። “የኢትዮጵያን የቀድሞ የግዛት ክልልና አደረጃጀት እንደነበረ አስጠብቀን፣ አማርኛ የመግባቢያ ብሄራዊ ቋንቋችን ሆኖ፣ ኢትዮጵያውያን ተብለን በጋራ መኖር እንችላለን”  ከሚለው ነባር አስተሳሰብ የተሻለ ወይም የተሻሻለ አሳብ አለው።  

ለአብነት “ኦሮምኛ የኢትዮጵያ ሁለተኛ ብሄራዊ ቋንቋ መሆን አለበት” ብሎ ሲያበቃ በትምህርት ቤትም ኦሮምኛ ቋንቋ መማር ለመላ ኢትዮጵያውያን ግዴታ መሆን እንዳለበት ያሰምርበታል። በመላ ኢትዮጵያ በተለይ ደግሞ በአማራ ክልል ተማሪዎች ከክፍል ወደ ክፍል ለማለፍ ኦሮምኛ ቋንቋን ማለፍ ወሳኝ መሆን አለበት። አንድ ኦሮሞ ከኦሮምኛና ከእንግሊዝኛ ባሻገር አማርኛ እንደሚማረው ሁሉ፣ አንድ አማራም ከአማርኛ እና ከእንግሊዝኛ ቋንቋዎች ባሻገር ኦሮምኛ መማር ግዴታው ሊሆን ይገባዋል። በርግጥ አንዳርጋቸው የኦሮምኛ ፊደል ጉዳይ ላይ ጥያቄ አለው። “ቁቤ ወይስ ግዕዝ?” የሚውን አንጠልጥሎ ተወው። 

አሳቡ ተፈፃሚ ከሆነ በአስር አመታት ጊዜ ውስጥ በህዝቦች መካከል ሊያመጣ ሚችለውን መተሳሰር በስሜት አወጋኝ። ጎንደር የተወለደ ወጣት ደምቢዶሎ ለስራ ሲሄድ ከአገሬው ሰው ጋር በመረጠው ቋንቋ መግባባት ይቻለዋል። በግልባጩ አንድ ኦሮሞ አማርኛ ከቻለ በመላ አገሪቱ ተዘዋውሮ ለመስራት አይቸገርም። በርግጥ “የኔን ዳንስ ብቻ ደንሱ፣ የኔን እጀ ጠባብ ብቻ ልበሱ! የኔን አምባሻ ብቻ ቁረሱ!” የሚለው አስተሳሰብ በዘመናችን ተቀባይነት የሌለው መሆኑ እውነት ነበር።  

የወያኔን የክልል አወቃቀር አንዳርጋቸው አይደግፍም። “ከፋፋይ፣ ውሎ አድሮ በዘር ላይ ለተመሰረተ ግጭት በር የሚከፍት።” ይለዋል። በተጨማሪ ለአስተዳደር የማይመች ይለዋል። ስለዚህ የአገሪቱ ግዛት ለአስተዳደር፣ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት በሚመች መልኩ እንደገና መዋቀር እንደሚኖርበት ይገልፃል። ትግራይ እና የሶማሊያ ክልል እንደነበረ ሊቀጥል ይችል ይሆናል። “ኦሮምያ” እና “አማራ” ተብለው የሚታወቁት ክልሎች ግን እንደገና መሰራት ይኖርባቸዋል። ኦሮምያ ለሶስት ሊከፈል ይችል ይሆናል። የአማራ ክልልም እንዲሁ ለሁለት ሊከፈል ይችላል። አንዳርጋቸው እንደሚለው ለኢኮኖሚ ግንባታና ለአስተዳደር በሚያመች መልኩ እንጂ ቋንቋን መሰረት ያደረገ አወቃቀር ለኢትዮጵያ ተመራጭ አይደለም። “ቋንቋን መሰረት ያደረገ ክልል ሳይኖር ቋንቋን መጠቀም የሚችሉ ማህበረሰቦች እንዲኖሩ ማድረግ ይቻላል።” ብሎ ያምናል። ከአስተዳደር አንፃር ሲናገርም፣ “የደብረብርሃን ነዋሪ የላይኛውን አካል ለማግኘት የአባይን በረሃ ማቋረጥ ግዴታው መሆን የለበትም። የደምቢዶሎ ሰው አዳማ ድረስ ለምን ይጓዛል?” ሲል ጠየቀ።  

በኔ በኩል ስለ መጪው ዘመን ማለት የምሻው አጠቃላይ ነገር አለ። ርግጥ ነው፣ በመጪው ዘመን አሸናፊ የሚሆነው ሃይል የተሻለ የፖለቲካ ብቃት ያለውና ጠመንጃ የታጠቀው ነው። የህዝብ ድጋፍ ብቻውን ስልጣን ለመጨበጥ እንደማያበቃ በተደጋጋሚ አይተናል። ከእውቀት እና ከንቃት ጋር ጠመንጃ ይዞ መገኘትን ይጠይቃል። በደርግ የውድቀት ዋዜማ አሜሪካኖች ኢህአፓን ያላሳተፉት ጠመንጃ ይዞ መሬት ላይ ባለመገኘቱ ነበር። ርግጥ ነው፣ ከላይ ከተጠቀሱት ሶስት ሃይሎች በተጨማሪ የወያኔን መንገዳገድ ተከትሎ ሊከሰት የሚችል ሁኔታ ይኖር ይሆናል። ምእራባውያኑ በአሜሪካ ፊታውራሪነት ኢትዮጵያን ተቆጣጥረው አገሪቱን በሞግዚት ለማስተዳደር ይሞክሩ ይሆናል። ምናልባትም አሜሪካኖች በተሳሳተ ግምገማ ብርቱካን ሚደቅሳን ወይም ስዬ አብርሃን በአሻንጉሊትነት ከላይ ለማስቀመጥ ያስቡ ይሆናል። 

ከአንዳርጋቸው ጋር ምፅዋ ላይ ተለያየን….
እኔ በጀልባ ወደ ዳህላክ ጉዞዬን ስቀጥል፤ የፅጌ ልጅ ምፅዋ ቀረ። ወደ ምፅዋ ለምን እንደመጣ አልነገረኝም። ከሰዎች ጋር የስራ ቀጠሮ እንዳለው ብቻ ነበር የጠቆመኝ።  

በኔ በኩል ወደ ዳህላክ የተጓዝኩት በቀጣይ ለምፅፈው መፅሃፍ ግብአት ለመሰብሰብ ነበር። እዚህ ብዙ ስራ አለብኝ። “የቡርቃ ዝምታ”ን ወደ ኦሮምኛ ማስተርጎም ከማደርጋቸው አንዱ ነው። ሌላም ብዙ ስራ አለብኝ። ተንጋዶ ሲፃፍ የኖረውን የአካባቢያችንን ታሪክ እያቃናሁ በስነፅሁፍ አቀርበዋለሁ። በምሰራው ስራ የሚበሳጩ ወገኖች የሚያሰሙት አደንቋሪ ጩኸት ረብሾኝ አያውቅም። ጎርኪይ ጥሩ አድርጎ መክሮኛል። ተቀናቃኞቹ እንደ ቡችላ እየተከታተሉ በጮሁበት ጊዜ፣ “በዝንብ የተወረረ ፈረስ መሰልኩ” ነበር ያለው። የኤልያስ ክፍሌ ብርታትም ጥሩ ትምህርት ይሰጣል። የሰው ልጅ በውግዘት ብዛት የሚሞት ቢሆን ኖሮ ዛሬ የኤልያስ መቶኛ የሙት አመት ይከበር ነበር። 

• • • 

ይህን አንቀፅ ስፅፍ ቀይባህር ከፊትለፊቴ ተዘርግቶ እያየሁ ነበር።

ሰማዩና ባህሩ ተገጣጥሞአል። ከዚህ ከጉርጉሱም የተነሳ ጀልባ ባህሩን ሰንጥቆ ከተጓዘ በሰአታት ውስጥ ሳዑዲ አረቢያ ይገባል። የአገር ውስጥ ቱሪስቶች ባህሩን ሞልተውታል። ብዙዎች ይዋኛሉ። አሸዋው ላይ የእጅ ኳስ የሚጫወቱም ይታዩኛል። በርግጥ ባህሩ ውብ ነው። በጣም ውብ ነው። በደም ታሪክ የታጠበ ቢሆንም ውሃው ንፁህና ሰማያዊ ነው። ኦሮሞዎች በሃብታም መሬታቸው፣ ኦጋዴኖች በዘይታቸው፣ ኤርትራውያን በባህራቸው ምክንያት በጦርነት እና በአፈና አዙሪት ውስጥ ብዙ መስዋእትነት ከፍለዋል። መላ የአፍሪቃ ቀንድ ህዝቦች አንዳችም ጥቅም ባላገኙበት ጦርነት ውስጥ ተሰውተዋል። የኢትዮጵያ መሪዎች 250 እስከ 300 ሺህ የሚገመት የሰው ሃይል ኤርትራ ምድር ላይ የሰውት የዜጋ ህይወት በዜሮ ተባዝቶአል። ምንም ትርፍ አልነበረውም። እና በቀይባህር ምክንያት ለዘመናት የዘለቀው አካባቢያዊ ጦርነት በኛ ዘመን አፉ መዘጋት አለበት። 

እንዳልኩት ቀይ ባህር ከፊቴ ተዘርግቶአል 

ህዳር እንደመሆኑ ምፅዋ ላይ ከባድ ዝናብ ሲረግጥ ቆየ። እንዲያም ሆኖ ማምሻው ላይ ስስ ሸሚዝ ብቻ ነበር የለበስኩት። ዝናቡ ሲቆም ሴንትራል ሆቴል ባህሩ ዳርቻ ቁጭ አልኩ። ሶስት ሰአት ሙሉ ተቀመጥኩ። አእምሮዬ ፀጥ ብሎ ነበር። ባህሩ ግን ፀጥ አላለም። ለብ ያለ ነፋስ ይነፍሳል። ማእበሉ ይገማሸራል። የባህሩ ነፋስ ለስላሳ ጣቶች ያለማቋረጥ ዳበሱኝ። አርጅቼ እስክሞት እዚህ ባህሩ ዳር መቆየትን እስክመኝ ድረስ ደስተኛ ነበርኩ። በርግጥም ወራሪዎች ይህን ባህር ለመቆጣጠር የከፈሉት መስዋእትነት ልባዊ ምክንያቱ በትክክል እየገባኝ ነበር። በርግጥ፣ ባህሩ በጣም ውብ ነው። 

ግልፅ እውነት አለ። ለጋራ ጥቅምና ሰላም ሲባል ኢትዮጵያውያን የቀይ ባህር ተጠቃሚ መሆን ይኖርባቸዋል። ወደብ ብቻ አይደለም። ወጣት ተማሪዎች በአውቶብስ ተጉዘው ባህሩ ላይ መዋኘት አለባቸው። ኤርትራውያንም እንዲሁ ወደ ሶደሬና ላንጋኖ። የመጪው ዘመን ትውልድ የኤርትራን ሉአላዊነት አምኖ በሰላምና በመከባበር ስለመኖር ማሰብ አለበት። ሌላ ምርጫ ያለ አይመስለኝም። አለ ከተባለም መግደልና መሞት ብቻ ነው። መሞትና መግደሉን ሞክረነዋል። ቁስሉና ኪሳራው የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው።  

• • • 

ከዳህላክ ወደ አስመራ ስመለስ ዶጋሊ (ዶግ አሊ) ላይ አንድ ሌሊት አደርኩ። ኮሎኔል ክሩስቶፈር እና ራስ አሉላ አባነጋ የተዋጉበትን ኮረብታ ተንተርሶ አንድ የመዝናኛ ማዕከል ተገንብቶአል። ከመዝናኛው ማእከል በስተጀርባ የበርበሬ እርሻ ላይን እስኪታክት ተዘርግቶ ይታያል። የዶጋሊ በርበሬ ከየመንና ከማረቆ በርበሬ የመረረ መሆኑን ሰምቻለሁ።ዶጋሊ አደርኩ’ ማለት እንኳ አልችልም። ሳይነጋ መንገዴን ቀጥያለሁ። በርግጥ እስከ ውድቅት ድረስ ጣልያኖች ለክሩስቶፈር ከተከሉለት የመስቀል ሃውልት አጠገብ በተዘረጋ የጠፍር አልጋ ላይ ጋደም ብዬ ነበር።  

ጨረቃዋ እንደ ፀሃይ ደምቃ ነበር።

ጋደም ካልኩበት አልጋ በአንድ ሜትር ተኩል ርቀት ላይ አፉን የከፈተ አለት አየሁ። አለቱ ስር የተጠቀለለ ነገር! በጨረቃው ብርሃን የተጠቀለለውን ነገር ምንነት ለማወቅ ሞከርኩ። በትክክል ጥቅሉ ነገር የበረሃ እባብ ይመስላል። በዚያችው ቅፅበት ሰውነቴ ቀዘቀዘ። ባላየው ኖሮ ሌሊት ነድፎ ይገድለኝ ነበር ማለት ነው? እንኳን ሳልተኛ አየሁት። አሁን ምንድነው ማድረግ ያለብኝ? መግደል? በትክክል! እባቡ መገደል አለበት። በተኛበት በድንጋይ መጨፍለቅ። መሆን ያለበት ይኸው ነው፣ 

“አቶ እባብ” አልኩ፣ በለሆሳስ።
ምናባዊ መልስ ሰጠኝ፣
“ጤና ይስጥልኝ ወንድሜ…”
“ከመሞትህ በፊት አንድ ሁለት ጥያቄ ልጠይቅህ?”
“ጠይቀኝ…”
“ቅድመ አያትህ ሄዋንን በማሳሳቷ ኩራት ይሰማሃል?”
አቶ እባብ አንገቱና ቀና አድርጎ ሳቀ።
“ሰዎች መቼም ትገርማላችሁ። የገዛ ተረታችሁ እስረኞች። ለፍርሃታችሁ መደበቂያ የሰበብ ጉድጓድ በመቆፈር ከቶ የሚወዳደራችሁ የለም።”
“እና ሄዋንን ማን አሳሳታት?”
“እኔ ምን አቅልሃለሁ?”
“አራት እግር ነበረህ የሚባለውስ?”
“እባክህ ተወኝ ወንድሜ! አራት እግር! ሃምሳ እግር! መቶ እግር! አሉባልታችሁን እናንተው ተዝናኑበት። ለእንዲህ ያለ ዝባዝንኬ እኔ ጆሮ የለኝም።”
“ምላስህ ግን መንታ ነው ይባላል።”
አቶ እባብ እንደገና ሳቀ።
“የናንተን ምላስ ካልመሰለ ውጉዝ ነው?”
“የመጨረሻ ጥያቄ ልጠይቅህ?”
“ጠይቅ!”
“ሰዎች ለምንድነው የሚጠሉህ?”
“ሰዎች ለበጎች እና ለውሾች ፍቅር አላቸው። ለምን ይመስልሃል? እኔ እንደ ውሻ አልረገጥም። እንደ በግ አንገቴን ዘርግቼ አልታረድም። ሊገድለኝ የሚመጣውን እኔም ከቻልኩ ቀድሜ እገድለዋለሁ። በተቀረ ከሰው ልጅ ጋር ምንም የሚያገናኘን ነገር የለም። ምግቤ አይጥ ነው። የዘራችሁትን ባቄላ ነክቼ አላውቅም።”
“የሰው ልጆች በመረረ ሁኔታ የሚጠሉህ ከመነሻው ለምንድነው?”
“ከሰይጣን ጋር ተስማምቶ ሄዋንን አሳሳተ ትላላችሁ። ርካሽ ፕሮፓጋንዳ! ድክመታችሁን ለመሸፈን የራሳችሁን የፈጠራ ተረት አምናችሁ የጥላቻ ዱላችሁን ጭንቅላቴ ላይ አሳረፋችሁ። እኔ ስለራሴ እንደማውቀው ግን ለሰው ልጅ ፈውስ ነኝ። የሰው ልጅ በሽታ መቼም አያልቅ። ልቡን፣ ኩላሊቱን፣ አንጎሉን፣ ሳንባውን፣ ጣፊያውን፣ አይኑን፣ ጆሮውን የህመሙ ብዛት ምን ማለቂያ አለው? ቁርጥማት፣ ሪህ፣ ማጅራት ገትር፣ ካንሰር፣ እብደት… ምኑቅጡ? የሰው በሽታ በመብዛቱ የእባብ ልጅ ወዝ እንደ ወተት እየታለበ ፈውስ ይሆናል። ፈውሱን መርዝ ትሉታላችሁ። እኛን ደግሞ ‘ፈውሰኛ’ ማለቱን ትታችሁ ‘መርዘኛ’ ትሉናላችሁ! እንደ ጥቅሜና የባህርይ አርአያነቴ ቢሆን የሰው ልጆች ስም፣ ‘ገብረአብ’ ሳይሆን፣ ‘ገብረ-እባብ’፣ ‘አንዳርጋቸው’ ሳይሆን፣ ‘እባብ-አርጋቸው’ መባል ነበረበት። ለነገሩ ከጥንቱም ቢሆን የሰው ልጅ የገዛ መድሃኒቱን የመግደልና የማውገዝ ልማድ ያዳበረ ፍጡር ነው። የሆነው ሆኖ፣ በል ድንጋይ አንሳና ውገረኝ! የአባትህ ወኔ ደምህ ውስጥ ካለ ተነስና ተጠጋኝ!” 

አይኔ ጨለማውን እየለመደው ሲሄድ እባብ የመሰለኝ ጥቅልል የበረሃ ሃረግ መሆኑን ተረዳሁ። ጨረቃዋ እንደ ፀሃይ ደምቃ ነበር። በርቀት ከታሪካዊው ኮረብታ ላይ የኤርትራ እና የኢጣሊያ ባንዴራዎች ሲውለበለቡ እያየሁ ጋደም አልኩ። ሰማዩና ምድሩ ውብ እና ሰላማዊ ነበር…

• • • 

አስመራ በደረስሁ ሰሞን የዳውድ ኢብሳ ባለቤት አረፈች። ሃዘን ለመድረስ ቤቱ ሄጄ ነበር። ለረጅም ጊዜ የማውቃቸውን የኦነግ ታጋዮች ከሃዘን ቤቱ አገኘሁዋቸውና ብዙ ተጨዋወትን። “የስደተኛው ማስታወሻ”ን አንስተን ስናወጋ ኦቦ ገመቹ አያና፣ “ጫልቱ እንኳን ሞተች።” አለኝ። አያያዘና አከለበት፣ “… ከዚያ ሁሉ ቀውስ በሁዋላ በፍፁም በህይወት መኖር አትችልም ነበር። በቁም ሞታ ነበር። ስጋዋ ከመንቀሳቀሱ በቀር ነፍስ አልነበራትም። አንብቤ ስጨርስ በጫልቱ መሞት ከፍተኛ እረፍት ተሰማኝ።” 

በርግጥ መራራ እውነት ከፊታችን አለ። እኛ ወደ መራራው እውነት መጠጋት ባንፈልግም፤ መራራው እውነት እንደ ኦሮሚያ ፈረሰኛ ወደኛ ትውልድ ሽምጥ እየጋለበ ነው። ኢትዮጵያን እንደ ሃገር ለማዳን የተሻለው አማራጭ ለመራራው እውነት እውቅና ሰጥቶ መደራደርና እርቅ መፈፀም ይመስለኛል። በኢትዮጵያዊነት ስም ለአንድ ወገን ባህልና ቋንቋ የበላይነት የሚታገሉ አክቲቪስቶች የጫልቱ ሚደቅሳ ህመም ቀድሞ ሊሰማቸው ቢችል ኖሮ የችግሩ ግማሽ ይቃለል ነበር። በአንፃሩ የጫልቱን የበደል ታሪክ መፃፍ “አማራና ኦሮሞን ማጋጨት ነው” ብለው የሚቀሰቅሱ ሰዎች ትርፍ አጊኝተውበታል ብዬ አልገምትም። አብዛኛው ኦሮሞ ጫልቱ ባለፈችበት መንገድ በመራመዱ ህመሙን ያውቀዋል። እና መካድም ሆነ ማድበስበስ አይቻልም። ጫልቱ ሚደቅሳ የኦሮሞ ህዝብ ላይ ለደረሰው ጭቋና ተምሳሌት ናት። ጫልቱ ላይ ለተፈፀመው ስርአታዊ ሽብር እውቅና መስጠት ሳይቻል በአፍሪቃ ቀንድ ህዝቦች መካከል እርቅና ሰላም ይወርዳል ብሎ ማሰብ የዋህነት ይመስለኛል።  

አጤ ምኒልክ በስልጣን ዘመኑ ስለፈፀመው ግፍ ሲነሳ አንዳንድ አክቲቪስቶች፣ “ያለፈ ነገር አታንሱ፣ ወደፊት ተመልከቱ፣ የታሪክ እስረኛ አትሁኑ!” በማለት ሲገስፁ ይሰማሉ። በግልባጩ ግን እነርሱ ጠዋትና ማታ ስለ “ቅዱስ ምኒልክ” ሲዘፍኑ ይሰማሉ። እነርሱ 150 አመታት ወደሁዋላ ተመልሰው ምኒልክን ሲያደንቁ ትክክል ሆኖ፤ ሌሎች ወደ ሁዋላ ተመልሰው የምኒልክን አገዛዝ ሲያወግዙ ስህተት የሚሆነው እንዴት ባለ ቀመር ይሆን? እነዚህ የአንድ ወገን አክቲቪስቶች እንዲህ ያለ ተቃርኖ ሲነሳባቸው በትክክል ምላሽ ሰጥተው አያውቁም። 

በወርሃ ጥቅምት አጋማሽ 2013 ከኦነግ ቃል አቀባይ ከቦሩ በራቃ ጋር ተገናኝተን ነበር። ያወጋናቸው ብዙ ጠቃሚ ርእሰ ጉዳዮች አሉ። ከተወያየንባቸው ነጥቦች መካከል የጫልቱ ሚደቅሳ ጉዳይ ዋናው ነበር። የጫልቱ ጉዳይ አቧራውን ባጨሰበት ምክንያት ላይ ተግባብተናል።ዱጋሳ በከኮን የማያውቅ፣ በሌንጮ ለታ ይደነግጣል!” እንዲሉ እኔ ስለራሴ እስከማውቀው የአማራ ህዝብ ባለውለታ ስለመሆኔ ነው። ሊመጣ የሚችለውን አደጋ፣ በርግጥም አሁን እየታየ ያለውን የአደጋ ፍንጭ አስቀድሜ፣የቡርቃ ዝምታላይ ጠቁሜ ነበር። አክራሪየአንድነት” ፖለቲከኞች ትምክህታቸውን ቀንሰው የመቻቻል ፖለቲካ እንዲጀምሩ መክሬያለሁ። አሁንም እመክራለሁ። አኖሌ ላይ የተፈፀመውን ጭፍጨፋ መካድ መፍትሄ አይሆንም። ድርጊቱ መፈፀሙን ማመን እና ዳዴኡኦ በገነባው ሃውልት ስር የይቅርታ እቅፍ አበባ ማኖር ይገባል። የተፈፀመውን መካድ ዋጋ የሚያስከፍል ይመስለኛል። በርግጥም ውጤቱን እያየነው ነው። Harma muraa Annoleeን እየዘፈነ የሚያድግ የኦሮሞ ልጅ፣ በተጨማሪ በአባቶቹ ላይ የተፈፀመው የሰቆቃ ታሪክ ሲካድ፣ መንጫ እንጂ እቅፍ አበባ ሊታየው አይችልም። ከዘረኝነቱ አረንቋ ለመውጣት “እርቅና መቻቻል” ያስፈልጋል። መቻቻል ማለት የሌላውን ወገን ስሜትና ፍላጎት በማስተዋል፣ የራስን ስሜትና ፍላጎት መመጠን ማለት እንጂ ሌላ ትርጉም የለውም።   

• • • 

2014 የመጀመሪያው ሳምንት የኔና የአንዳርጋቸው የጋራ ጓደኛ ራት ጋብዞን ነበር። ጓደኛችን “የስደተኛው ማስታወሻ”ን ማንበቡን ከገለፀ በሁዋላ እንደዋዛ የጫልቱ ሚደቅሳን ታሪክ አነሳ፣ 

“በኦሮሞዎች ላይ እንዲህ ያለ ነገር ይፈፀም ነበር? መረጃው እንግዳ ነው የሆነብኝ?” ሲል ጠየቀ። 

ምላሽ የመስጠት እድሉን ለአንዳርጋቸው ተውኩ። ርግጥ ነው በዚህ ጉዳይ ላይ በከፊልም ቢሆን ከአንዳርጋቸው ጋር እንደማንግባባ ግልፅ ነበር። አንዳርጋቸው ጫልቱ ላይ የደረሰው አይነት በደል በኢትዮጵያ ይፈፀም እንደነበር ካመነ በሁዋላ፣ ሆኖም ከተሜዎች የገጠር ሰዎች ላይ የሚፈፅሙት በደል እንጂ “አማሮች ኦሮሞዎች ላይ” ሊባል የሚችል እንዳልሆነ አብራራ። እዚህ ላይ ግን የማንክደው እውነት አለ። አንድ ከተሜ አማራ፣ ከገጠር የመጣ አማራ ላይ ቢያላግጥ ጉዳቱ ለክፉ አይሰጥም። አንድ ከተሜ አማራ ከገጠር የመጣ ኦሮሞ ላይ ካላገጠ ግን ማንነትን የሚነካ ዘረኛነት ስለሚሆን ጦርነት ሊነሳ ይችላል። ጥቁር አሜሪካውያን ርስበራስ “ኔግር” ቢባባሉም፣ ነጮች “ኔግር” ካሏቸው ግን ጩቤ ይመዛሉ።

እይታዬን በዚህ መልኩ ገለፅኩ።

ዞረም ቀረ በመጨረሻ የሚቀረውና የሚሻለው መነጋገርና መግባባት ነው። በመሰረቱ ለተፈፀመው በደል እውቅና መስጠት ሳይቻል እርቅ ሊመጣ አይችልም። ማንዴላም ቢሆን ከነጮቹ ጋር ለመታረቅ የበቃው ዘረኞቹ ነጮች ለፈፀሙት በደል እውቅና ሰጥተው፣ ይቅርታ ከጠየቁ በሁዋላ ነበር።  

የራት ላይ ንግግራችን በወዳጅነት መንፈስ የሚካሄድ ስለነበር ለተነሳው ጉዳይ እልባት መስጠት የግድ አልነበረም። እንደተንጠለጠለ በመተው ወደ ሌላ ርእሰ ጉዳይ ተሻገርን። ጋባዣችን “የማርታ ብልግና” የተባለውን ታሪክ አስታውሶ መሳቅ ጀመረ። 
• • • 

እነሆ! በመጪው መጋቢት 2014 ወደ ኦምሃጀርና ወደ ሓሬና እሄዳለሁ። የአርበኞች እና የግንቦት 7 ሰራዊት ካሉባቸው አካባቢዎች እሰነብታለሁ። የኦነግ እና የኦጋዴን አማፅያን ወዳሉባቸው ተራሮችም አቀናለሁ። ርግጥ ነው፣ የዘመናችንን የድልም ሆነ የውድቀት፣ የትግልም ሆነ የለበጣ እውነተኛ ታሪክ ለመጪው ትውልድ ማስቀረት የሚቻለው በቦታው በመገኘት ይመስለኛል። Nama jaallattus nama jibbitus hubattee hin ilaaliin ይላል የቱለማ ኦሮሞ ሲተርት። “የምትጠላውንም ሆነ የምትወደውን ሰው አተኩረህ አትመልከት” እንደ ማለት ነው። ለምን ቢባል ከምትጠላው ሰው ልብ ውስጥ የምትወደውን ነገር ልታገኝ ትችላለህ። ከምትወደው ሰውም እንዲሁ በተቃራኒው። በርግጥ ይህ ተረት እንደኔ ላለው ፀሃፊ አይሆንም። እውነትን ለመፃፍ አተኩሮ መመልከቱ ያዋጣኛል።

እንግዲህ ስለነገ አንዳች አናውቅም።
ስለ ነገ ለማወቅ ግን እንጓጓለን።
እና ነገ ምን ይከሰታል?  

በአባ ታጠቅ ካሳ ዘመዶች የተገነባው የአንዳርጋቸው ጦር፣ ከ“አርበኞች”ና ከ“ዴምሕት” ጋር ግንባር ፈጥሮ በጌምድርን ሲቆጣጠር፣ “የቋራው አንበሳ - በ200 አመቱ ቢያገሳ - ስንቱን! ቀሰቀሰውሳ” የሚል ነጠላ ዜማ እያዜመ ከሰሜን አሜሪካና ከአውሮፓ፣ ወደ ጎንደር የሚፈስ የብረት ጎርፍ በአሳብ ማየት ይቻል ይሆን? ወይ ደግሞ ኦነግ (ABO) ሌንጮና ዲማን ሸገር ላይ አስቀድሞ በስውር ተክሎ ሲያበቃ፣ በባሌና በሶማሌ ግንባር ብቅ ይል ይሆን? ኦነግ Odaa ባንዴራውን በጋራሙለታ እና በጭላሎ ተራሮች አናት ላይ እየተከለ፣ Harma muraa Annoleeን እየዘፈነ ወደ ፊንፊኔ ሲገሰግስ በአይነ ህሊናችሁ ተመልከቱ። አሊያም ይልቃል ጌትነት ሳይቀደም ቀድሞ፣ በአራዳውና በፈረሰኛው ጊዮርጊስ እርዳታ፣ ሲተከል እንጂ ሲወረወር የማይታየውን ሰማያዊ ጦር ወርውሮ የወያኔን የልብ ትርታ ማቆም ከቻለ፣ እንደምኞቱ ነብርና ፍየል ተደጋግፈው የሚተኙባት፣ ሰላም ቁርሷ፣ ፍቅር ምሳዋ፣ እስክስታ ራቷ የሆነች ሰማያዊት ኢትዮጵያን ያለምንም ደም መመስረት ይቻለው ይሆናል። ነገን ማንም አያውቃትም! ምናልባት ይህ ሁሉ ወግ የእሳት ዳር ተረት ሆኖ ሲያበቃ፣ የዳግማዊ ወያኔ የልጅ ልጆች፣ ሳልሳዊ ወያኔ ተብለው እስከ 3000 ምእተ አመት በጠመንጃ እየቀጠቀጡ ሊገዙ ይችላሉ።  

በዚያም ተባለ በዚህ በመሞትና በመግደል መንገድ መጓዙ ለማናችንም ቢሆን አይበጅም። የጦርነት መንገድ የመጨረሻ አማራጭ ነው። ወደ መጨረሻው አማራጭ ላለመድረስ የተደረገው ሙከራ በተደጋጋሚ መክሸፉ ያሳዝናል። በጣም ያሳዝናል። ቢቻል አሁንም የመጨረሻውን አማራጭ ላለመጠቀም መሞከር ይገባል። ርግጥ ነው፤ መጪውን ዘመን አውቆ የሚያሳውቅ ነብይ መውለድ አልተቻለም። ለነገሩ ነቢይ መውለድ የተቻለበት ዘመንም አልነበረም። እንግዲህ በህይወት እስካለን የኖርነውንና ያወቅነውን እየፃፍን እናዘግማለን…  

 


 

No comments: