Monday, January 5, 2015

የሌንጮ ለታ መንገድ


ከተስፋዬ ገብረአብ (Gadaa)

ቦ ሌንጮ ለታ ለ2015 ምርጫ እየተጓዘ ነው። በባላንጦቹ እጅ ወደ ወደቀች አባት አገሩ እየተጓዘ ነው።ከዚሁ ዜና ጋር በተያያዘ ከብዙ የፖለቲካ ሰዎች ጋር ተወያይቼአለሁ። ሌንጮ መግባቱን በጥብቅ የሚደግፉ አሉ። በጥብቅ የሚቃወሙም አሉ። ሁለቱም ወገኖች አሳማኝ የሚመስል ትንታኔ ያቀርባሉ።

“ሌንጮ ማድረግ የመቻል አቅሙ ከፍተኛ በነበረበት ዘመን እድሉ አምልጦታል። አሁን ወደ አገር ቤት ቢገባም ባይገባም ተፅእኖ ማሳደር ስለማይችል ለውጥ አያመጣም።” በሚል ግዴለሽ የሆኑም አጋጥመውኛል።

ከአመታት በፊት ጀምሮ በሌንጮ ጉዳይ ላይ ስፅፍ ቆይቻለሁ። ከፃፍኳቸው መፃፅፎች መካከል፣ “የቤተመንግስት ሹክሹክታ” የሚለው ሊጠቀስ የሚችል ሲሆን፣ ትረካው ሌንጮ ኦህዴድን በርካሽ ዋጋ ሊገዛ ከወያኔ ጋር መደራደሩን ይጠቁም ነበር። ከሹክሹክታና ከግምት በቀር አሁንም ቢሆን ሌንጮ ምን ጥቅም ለማግኘት ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገባ በትክክል አልተነገረንም። በመሆኑም በዚህ መፃፅፍ አንዳንድ ነጥቦችን በጨረፍታ አነሳለሁ...
“ሌንጮ ወደ አገር ቤት የሚገባ ከሆነ፣ ከወያኔ ጋር በሚያደርጋቸው ድርድሮችየታሰሩ የኦሮሞ የፖለቲካ እስረኞች ቀዳሚ አጀንዳዎቹ ሊሆኑ ይገባል።” የሚሉ አሉ።

ርግጥ ነው፤ ሌንጮ የOLF አመራር አባል ከነበረበት ጊዜ ጀምሮ የታሰሩ ኦሮሞዎች አሁንም ፍትህ ተነፍገው በእስር ላይ ይገኛሉ። በሌንጮ አመራር ዘመን በፈፀሙት ድርጊት የተያዙ የOLF ታጋዮች እስርቤት ተዘግቶባቸው ሳለ፤ ሌንጮ ፊንፊኔ ላይ በነፃነት ቢዘዋወር ለህሊና ይጎረብጣል። ሆኖም በዚህ ወቅት ሌንጮ የOLF የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ ወያኔ ላይ ተፅእኖ ለማሳደር የሚያበቃ አቅም የለውም። ስለዚህ ከሌንጮ የሚጠበቀው የማድረግ አቅሙን ማሳደግ ነው። ለአብነት አሸንፎ ወደ ፓርላማው መግባት ከቻለ በፓርላማ ቆይታው የእስረኞቹን ጉዳይ በማንሳት ተፅእኖ ለማሳደር ይቻለው ይሆናል።

“ሌንጮ ሲቪል ሰራዊቱን አስከትሎ ኢትዮጵያ በመግባቱ ወያኔ ይጠቀማል ወይስ ይጎዳል?” የሚለው ሌላው ጥያቄ አከራካሪ ጥያቄ ሆኖ ወደ መድረክ መጥቶአል።

ኢትዮ አማራ ፖለቲከኞች በአብዛኛው የደገፉት አይመስሉም። ከሚፅፏቸው መፃፅፎች ለመረዳት እንደቻልኩት፣“ለወያኔ የውሸት ምርጫ እውቅና ከመስጠትና አጃቢ ከመሆን ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም።” ሲሉ ያናንቁታል።በተመሳሳይ፣ “በሌንጮ መግባት ወያኔ ጊዜያዊ ጥቅም ያገኛል።” የሚሉ ወገኖች፣ “OLFና የአንድነት ሃይሎችን ያዳክማል” ብሎ ወያኔ አስቦ ከሆነ በርግጥ ፍርፋሪ ጥቅም ያገኛል። ወያኔ በአንድነት ሃይሎች ስጋት ካለው ለሌንጮ ቡድን ለቀቅ ያለ ስልጣን በመስጠት፣ ኦሮሚያ በአንፃራዊነት ጠንካራ ክልል እንዲሆን በመፍቀድ የሃይል ሚዛኑን ለማስተካከል ይሞክር ይሆናል።

በብሄር የተደራጁ ሃይሎች፣ “ከዚህ በሁዋላ የቀድሞ የአማራ ገዢ መደብ ናፋቂዎችና ወራሾች ወደ ስልጣን የመምጣት እድል ማግኘት የለባቸውም።” የሚል አቋም ስላላቸው፤ የአማራ ፖለቲከኞች ጠንክረው መታየት ሲጀምሩ ታክቲካዊ ትብብር ሊያደርጉ እንደሚችሉ የሚታመን ነው። በቅንጅት መበርታት ጊዜ “ህብረቶች” የወሰዱት የመለሳለስ አቋም ለአባባሌ አስረጅ ሊሆን የሚችል ነው። በርግጥ ወያኔና ሌንጮን ሊያቀራርባቸው የሚችል አንድ ስትራቴጂያዊ አጀንዳ ከተገኘ የኦህዴድ ግማሽ ጎን ለሌንጮ በርካሽ ሊሸጥለት ይችላል። ይህን ግምት ባለመደገፍ፣ “ወያኔ ይህን ካደረገ ራሱን እንደገደለ ይቆጠራል።” የሚሉ አሉ። በርግጥ ወያኔ በስልጣን መቀጠል እንደማይችል እርግጠኛ ሲሆን፤ አሟሟቱን ለማሳመር መሞከሩ አይቀርም።

ይህ ትንታኔ ውሃ ማንሳት ካልቻለ ሌላውን ጎን ማየትም ይቻላል።

መረጃው የተጨበጠ ባይሆንም ሌንጮ ወደ አገርቤት እየገባ ያለው በ2015 ምርጫ እንዲሳተፍ አሜሪካውያን ወያኔ ላይ ተፅእኖ በማድረጋቸው መሆኑን በጓሮ መስኮት በኩል ስንሰማ ቆይተናል። የወያኔ መንግስት በአሜሪካ የበጀት ድጎማ የሚንቀሳቀስ እንደመሆኑ፤ ሌንጮን በምርጫ እንዲያሳትፍ ተፅእኖ ተደርጎበት ሊሆን ይችላል። ይህ ከሆነ ሁለቱም የአሜሪካውያንን ፍላጎት ለመርካት ይሰራሉ ማለት ይሆናል። ወያኔ ሌንጮን የሚቀበለው ተገዶ ከሆነ፤ከወያኔ ነባር ባህርይ በመነሳት ቀጥሎ ሊሆን የሚችለውን ከወዲሁ መገመት አይገድም። አጀማመሩ ላይ ODF በነፃነት እንዲንቀሳቀስ ወያኔ ይፈቅዳል። የዲማና የሌንጮንበነፃነት መንቀሳቀስም ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታና ከምእራባውያን ድጋፍ መለመኛ ያደርገዋል። ከሌንጮና ከዲማ ስር የሚሰሩትን አባላትና ካድሬዎችግን ማሳደድ፣ ማሰርና መግደሉን ይቀጥላል። ቡልቻ ደመቅሳ እና መረራ ጉዲና ላይ ሲፈፅሙ የኖሩትን፤ ሌንጮና ዲማ ላይም በመድገም ተስፋ ሊያስቆርጧቸው መሞከራቸው የማይቀር ነው። ያም ሆኖ የሌንጮጉዞ በዜሮ ሊባዛ አይችልም። ሌንጮና ዲማ አንዳች ከመስራታቸው በፊት ወደ እስርቤት ቢላኩ እንኳ በግልባጩ ጥቅም እንጂ ጉዳት አይሆንም። በገዢዎቹ አፈና ምክንያት በምሬት ላይ ያለው የኦሮሞ ህዝብ ለአመፅ የማቀጣጠያ ቤንዚን ያገኛል።

“ሌንጮ ድብቅ አላማ ይኖረው ይሆን? ለግል ዝናው እየሰራ ይሆን? ከቀድሞ የትግል ጓዶቹ ጋር እልህ ተጋብቶ በተሳሳተ መንገድ እየሰገረ ይሆን?” የሚሉ ሽው የሚሉ ጥያቄዎችም አሉ።

በአንድ ነገር ርግጠኛ መሆን ይቻላል። የሌንጮ ጉዞ ስልጣን ወይም ሃብት አሊያም ዝና ፍለጋ ሊሆን አይችልም። በፍፁም ሊሆን አይችልም። ሌንጮ በአንድ ወቅት ሬድዮ ላይ ቀርቦ እንደቀለደው ወደ አገርቤት ለመግባት የወሰነው ስደት ሰልችቶት ወይም የኖርዌይ በረዶ አንገፍግፎት ሊሆንም አይችልም። ሌንጮ ሙሉ ህይወቱን ለኦሮሞ ህዝብ አርነት የታገለ ታጋይ እንደመሆኑ የዚህ ጉዞው አላማም በተመሳሳይ አላማ ሊታይ የሚችል ነው። ሌንጮ ከነሙሉ ችግሮቹ ህይወቱን ለኦሮሞ ህዝብ የሰዋ ታጋይ ነው። በተደጋጋሚ ስህተቶች ፈፅሞ ሊሆን ይችላል። ከአንድ ጊዜ በላይ የተሳሳተ የትግል ስልቶችን ተከትሎ ሊሆን ይችላል። ያልተረጋገጡ ቢሆኑም በሌንጮ ላይ ብዙ ውንጀላዎችና ክሶችን ስንሰማ ኖረናል። በዚያም ተባለ በዚህ የተፈፀመው ሁሉ በትግል ሂደት ላይ ነው። ለድል የበቁ ታጋዮች በትግል ሂደት የፈፀሙት ስህተት ለመጨረሻው ግብ መሳካት ሲባል እንደተፈፀመ ይታመንላቸዋል። ያልተሳካላቸውም ተመሳሳዩን እድል የማግኘት መብት አላቸው። ማለትም የተፈፀመው ሁሉ ለኦሮሞ ህዝብ አርነት ሲባል እንደተፈፀመ ማመን ይገባል። በሌላ አነጋገር ተጠያቂነታቸውን ለታሪክ መተው ይገባል። በመሆኑም በዚህ ወቅት የሌንጮን ለጉዞ መነሳት በተለያዩ ምክንያቶች አለመደገፍ ለኦሮሞ ህዝብ ይጠቅማል ብዬ አላምንም።ሌንጮ የታሪክ ተወቃሽ የሚሆነው፤ ኖርዌይ በረዶ ውስጥ በሽማግሌዎች ማገገሚያ ካምፕ ውስጥ ተቀብሮ ቢቀር ነበር። አንድ አባባል አለ። በመሮጥ ላይ ሳለህ ብትወድቅ ስህተት አይደለም። መነሳት እየቻልክ በዚያው ወድቀህ ከቀረህ ግን የስህተቶች ሁሉ ቁንጮ ስህተት ይሆናል።

የኦሮሞን ህዝብ አፍነው ብዝበዛቸውን ለመቀጠል የሚመኙ ወገኖች ምኞታቸው ይሳካ ዘንድ ተስፋ የሚያደርጉት በኦሮሞዎች መከፋፈል ብቻ ነው። የሰሜን ሃበሻ ፖለቲከኞች በቀድሞው መንገድ ለመጓዝ ሌላ ተስፋና አቅም የላቸውም።በመሆኑም የኦሮሞ ህዝብ በጎሳና በሃይማኖት እንዲከፋፈል፣ በፖለቲካ አመለካከቱ እንዳይተማመን ጠንክረው ሲሰሩ ቆይተዋል። እነዚህ የፖለቲካ ሰዎች የኦሮሞን ህዝብ አዳክመው ለማቆየት ሲሉ የከረረ ልዩነቶቻቸውን እንኳ ችላ በማለት ታክቲካዊ ትብብር እስከማድረግ ሊሄዱ ይችላሉ። በመሆኑም የኦሮሞ ህዝብ አንድ ጥይት ሳይተኩስ፣ ህብረት በማሳየት ብቻካሰበው ግብ መድረስ ይቻለዋል።

ሌንጮ ODF ነኝ ብሏል። OLF ከመሆን ግን አያመልጥም። ማንኛውም ኦሮሞ ልቡOLF ነው። OLF ማለት ከፖለቲካ ግንባር በላይ ለኦሮሞ ህዝብ መንፈስ ሆኖአል። የOLF ህያው ሆኖ መቆየት የኦሮሞ ህዝብ የአርነት ትግል ሻማ እየተውለበለበ እንዲቆይ ማድረግ ማለት ነው። ወያኔ OLFን በመስጋት ብቻ ከኦሮሞ ህዝብ ጥያቄዎች ግማሹን ያህል መልሶታል። የODF ፊንፊኔ መግባት OLFን ይጠቅመዋል። በተመሳሳይOLF ጠመንጃ እና ባዙቃውን ይዞ መቆየቱODFን በጣም ይጠቅመዋል። OLF ለODF የማስፈራሪያ ወንድም ጋሻው ነው። ወያኔ  OLFን ለማዳከም ሲል የኦሮሚያን ሜዳ ለODF ለመልቀቅ ከተገደደ ለኦሮሞ ህዝብ ጥቅም ነው። የኦሮሚያን ስልጣን ከሙክታር ወደ ሌንጮ ወይም ወደ መረራ ማዛወር ከተቻለ የተሻለ ጥቅም ነው። ድርጅቶቹ ለኦሮሞ ህዝብ ባላቸው ወገናዊነት ይመዘናሉ።

ከመቶ የማይበልጡ ጓደኞቹን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ለመግባት የተዘጋጀው ሌንጮ፤ በአንድ አዳር ከመቶ ሺህ ያላነሰ አባልና ደጋፊ ሊያጥለቀልቀው እንደሚችል ከወዲሁ መገመትና መዘጋጀት መቻል አለበት። OLF በ1991 አዲሳባ ሲገባ የገጠመው ችግር ይኸው ነበር። ደጋፊዎቹን በአግባቡ ለማስተናገድ የሚያበቃ በቂ የካድሬ ሃይል አልነበረውም። የሃይሉ ሻውል CUD በ2005 ተመሳሳይ ችግር ገጥሞታል። OLF በሃገር ውስጥ በይፋ ለመንቀሳቀስ ህጋዊ እውቅና ስለሌለው፤ የሚያረካ መጠለያ ያጣው የኦሮሚያ ወጣት የሌንጮና የዲማን መግባት እንደ በረከት ሊያየው ስለሚችል ODF ብዙ ጠቃሚ ስራ ለመስራት እድል ያገኛል።

“ዳያስፖራ ኦሮሞ ከሌንጮ መንገድ አንፃር አቋሙ ምን መሆን አለበት?” የሚለው ጥያቄ የዚህ መፃፅፍ ማእከላዊ ነጥብና መደምደሚያ ነው።

በመላ አለም የሚገኙ ኦሮሞዎች ሌንጮን በክብር ለመሸኘት መዘጋጀት ያለባቸው ይመስለኛል። እንደ ኦሮሞ ህዝብ ጥንታዊ ባህል የአቅማቸውን ያህል ለመንገድ የሚሆን ስንቅ ሰንቀው፤ ኦቦ ሌንጮ ለታን በክብር ወደ ኦሮሚያ ሊሸኙት የሚገባ ይመስለኛል። ኢትዮጵያ የሚገኝ ኦሮሞ ወጣትም ሌንጮ ለታን በክብር ለመቀበል መዘጋጀት አለበት። ሌንጮ የበለጠ ሃላፊነት እንዲሸከም ማድረግ የሚቻለው፤ ለህዝብ ጥቅም እንዲሰራ ይበልጥ ማጀገን የሚቻለው በዚህ መንገድ ብቻ ነው። ODFን መደገፍ ማለት OLFን መቃወም ማለት አይደለም። OLF ባዙቃ እና ጠመንጃውን እንደያዘ በቦታው አለ። ሌንጮ ለጊዜው ጠመንጃውን አስቀምጦ እድሜው በሚፈቅደው መጠን ለመታገል ወደ አባት አገሩ እየገባ ነው። ሌንጮ ለታ ጠመንጃውን ይዞ በኦሮሚያ ተራሮች ላይ የኖረባቸው ዘመናት አይደመሰሱም። ህያው ሆነው በኦሮሞ ህዝብ ታሪክ እና ልብ ውስጥለዘልአለሙ ይኖራሉ።
www.tgindex.blogspot.comየቅዳሜ ማስታወሻ፣የሌንጮ ለታ መንገድ Gadaa Ghebreab, January 5 2015 Email: ttgebreab@gmail.com

9 comments:

Anonymous said...

What a great analysis!

Anonymous said...

himm you are truly an amazing author. you spoke my mind, thank you dear brother.

Anonymous said...

This is what I have always been talking about. Thanks Gadaa. OLF and ODF are mutually reinforcing. Some Oromo nationalists think the other way.

Thank you!

asba said...

A very good analysis. Gadaa keep it up!
The time will when you enjoy your Bishoftuu too.

Anonymous said...

Gaddada!

Unknown said...

You are absolutely right bro.

I am already convinced that Obbo Lencoo Lata's ODF can be a positive option after I listened to this interview. Listen and be challenged everybody!

http://m.youtube.com/watch?v=LLMVzeX6mxI&feature=youtu.be

Anonymous said...

Abyssinians have been wedging wars and committing crimes against Oromo and the South for centuries. They will never surrender it for free. Coexistence as equal citizens of same nation has never been in their collective psyche. Oromo lost its freedom to war and will regain it through victory of same game. Stars will align for Oromo Nation during our life time.

Anonymous said...

rely all of u r fool, always he is talking about oromo,s people u know why he become selective on one ethnic group?
1. he knows abt them more than any ethnic group.
2. simply he can to convince them by telling a fake story... u can to take as a simple example yeburqa zimta and fake story of helen on the area of gelan.... we can to refer all his books, even he is trying to describe him self as a part of oromo by taking z place of a fox.
3. he get acceptance by hi fake novels than other ethnic group.
dont become fool we are talking abt a country not amhara, oromo, tigre, afar and so on... we are talking abt Ethiopia, a result of so many scarification and ups and downs a country of ...Tewodros, Yohannes, Minilik, Haileselassie..., ...Abune Petros, Belay Zeleke, Abidisa Aga,...all r their own + and - sign but still we believe they create a unified Ethiopia. but today tesfaye g/ab and other trying to divide Ethiopia and to maximize their country advantage/ertrea/ by talking a fake story.

Anonymous said...

Where is Tesfaye gebreab? His last article is at the end of January 2015, is something happen to him?